መስከረም 29፣ 2009
በሚንስትሮች ምክር ቤት የተጣለው የአቸስኳይ ጊዜ አዋጁ በመላ ሀገሪቱ የሚተገበር ቢሆንም በቀጣይ በልዩ ትኩረት የሚተገበርባቸው ቦታዎች በጠቅላይ ሚንስትሩ በሚመራ ኮማንድፖስት ይፋ እንደሚደረግ የፌደራል ጠቅላይ አቃቤ ህግ አቶ ጌታቸው አምባዬ ገለፁ።
የአቸስኳይ ጊዜ አዋጁ መተግበር ያለበት በሚል የሚያስቀምጣቸውን ጉዳዮችም ጠቅላይ አቃቤ ህጉ አብራርተዋል።
አዋጁን የሚያስፈፅመው ኮማንድ ፖስትም ህገ መንግስታዊ ስርዓቱን ለማስጠበቅና የዜጎችን ሰላማዊ ህይወት ለማስጠበቅ የሚያስችሉ እርምጃዎችን ሊወስድ ያስችለዋል ብለዋል።
ሁከትና ብጥብጥ መፍጠር፣ሰልፍ መውጣት፣ ማተምና ማሰራጨት እንዲሁም በምልክት መግለፅ በአቸስኳይ ጊዜ አዋጁ የሚከለከሉ እንደሆኑ ጠቅላይ አቃቤ ህጉ ገልፀዋል። የመገናኛ ዘዴዎችን እንዲዘጉ ማድረግ ፣መሰብሰብና ሰልፍ መከልከል ፣ ተጠርጣሪዎችን ያለፍርድቤት ትዕዛዝ መያዝና ፍተሻ ማድረግ ከብዙ በጥቂቱ አዋጁ ከሚፈቅዳቸው መካከል እንደሚገኝበት ተመልክቷል።
እነዚህንና መሰል ድንጋጌዎችን ጥሰው የተገኙና አዋጁን ለማስተግበር የሚንቀሳቀሱ የፀጥታ ኃይሎች የማይተባበሩ የህብረተሰብ ክፍሎች ተጠያቂ የሚሆኑበት ስርዓት መኖሩንም ጠቅላይ አቃቤ ህግ አቶ ጌታቸው ገልፀዋል።
በመላ አገሪቱ የተደነገገው የአቸስኳይ ጊዜ አዋጅ በቀጣይ በጠቅላይ ሚንስትሩ የሚመራው ኮማንድ ፖስት ይፋ በሚያደርጋቸው ቦታዎች ሊገደብ እንደሚችልም ገልፀዋል።
የአቸስኳይ ጊዜ አዋጁ ከታወጀበት ከመስከረም 28፣ 2009 ጀምሮ ለቀጣይ ስድስት ወራት የሚቅጥልና እንደ አስፈላጊነቱ ሊያጥርም ሊረዝምም የሚችል መሆኑንን ጠቅላይ አቃቤ ህጉ ተናግረዋል።
የኢፌዲሪ ህገ መንግስት አንቀፅ 93 የአቸስኳይ ጊዜ አዋጅ የሚደነገግባቸውን መሰረታዊ ምክንያቶችን ሲያስቀምጥ የውጭ ወረራ ስያጋጥም፣ የተፈጥሮ አደጋ ሲደርስ፣የሰዎች ጤንነትን አደጋ ላይ የሚጥል ወረርሽኝ ሲከሰትና ህገ መንግስታዊ ስርዓቱን አደጋ ላይ የሚጥል ሁነት ሲገጥም እንደሆነ ይገልፃል።ይህንኑ መሰረት በማድረግ ነው የሚኒስትሮች ምክር ቤትም የአቸስኳይ ጊዜ አዋጁን ማወጁን ይፋ ያድረገው።
ሪፖርተር፥ ብሩክ ያሬድ
![14657407_2112634918961081_928749022152011123_n](https://i0.wp.com/www.maledatimes.com/wp-content/uploads/2016/10/14657407_2112634918961081_928749022152011123_n.jpg?resize=565%2C409&ssl=1)
Average Rating