በህወሃት የበላይነት የሚመራው አገዛዝ እየገጠመው ያለውን ተቃውሞ ለመቆጣጠር ደፋ ቀና እያሉ ካሉ ከፍተኛ አመራሮች መካከል በረከት ስሞኦንና አዲሱ ለገሠ የብአዴንን የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴ ለመከታተል ባህር ዳር ከተማ መክተማቸውን ከውስጥ አዋቂ ምንጮች ለትንሳኤ ሬዲዮ ዝግጅት የደረሰው መረጃ አመለከተ።
የብአዴን የቀድሞ አመራሮች የነበሩ በረከት ስሞኦንና አዲሱ ለገሠ አለቃቸው መለስ ዜናዊ በህይወት በነበረበት የመጨረሻዎቹ አመታት መተካካት በሚለው የወያኔ ፖሊሲ የክልል ሥልጣናቸውን ለአዳዲስ የፓርቲው አባላት አስረክበው ወደ ፈደራል የተዛወሩ መሆናቸው ይታወቃል። ሆኖም ግን በአማራ ክልል የተቀሰቀሰው ህዝባዊ ተቃውሞ ከተጀመረ ወዲህ ህብረተሰቡን ለማረጋጋትና አሜን ብሎ ለስርዓቱ እንዲገዛ ለማድረግ ወደ ተለያዩ ከተሞች በመጓዝ የሃይማኖት አባቶችን፤ የአገር ሽማግሌዎችንና ወላጆችን በማነጋገር ሥራዎች ላይ ተጠምደው እንደሚገኙ ይነገራል።
በተለይ የወልቃይት የማንነት ጥያቄን ተከትሎ በተነሳው ተቃውሞ አንዳንድ ከፍተኛ የብአዴን አመራር አባላትና አብዛኛው ካድሬ ከህብረተሰቡ ጋር የመወገን አዝማሚያ አያሳየ ነው የሚል ስሞታ በእነ አባይ ወልዱ መቅረብ ከጀመረ ወዲህ የድርጅቱን እንቅስቃሴ ለመከታተል ይቻላቸው ዘንድ ሁለቱም ባለሥልጣኖች መቀመጫቸውን ወደ ባህር ዳር ማዞራቸው በበርካታ የብአዴን አመራሮች መካከል ተቃውሞን እያስነሳ እንደሆነ ይሰማል።
ብአዴን ውስጥ ለአመታት የኖረውን የህወሃት የበላይነት አጥብቀው የሚቃወሙና እራሳቸውን ነፃ ለማድረግ የቆረጡ አመራር አባላት ከወረዳ እስከ ክልሉ ባሉ መዋቅሮች ውስጥ እየበዙ መምጣታቸው የህወሃት አመራርን ክፉኛ እያስደነገጠ እንደመጣ የሚናገሩ ምንጮች በረከት ስሞኦንና አዲሱ ለገሠ ይህንን ጸረ ህወሃት እንቅስቃሴ ለመቆጣጠር ተልዕኮ እንዳላቸው ይገልጻሉ።
እራሳቸውንና ድርጅታቸውን ከህወሃት ለማላቀቅ እየሰሩ ያሉ የብአዴን አመራሮችና እስከ ወረዳ የሚዘልቀው አባላቱ እስከ ዛሬ የረባ እርምጃ ባለመውሰዳቸው እየተነቀፉ ናቸው። የበረከት ስሞኦንና አዲሱ ለገሠ በባህር ዳር መክተም ይህንን እንቅስቃሴ ሙሉ በሙሉ ለማጥፋት የሚያስችል ሴራ በድርጅቱ መካከል ለመትከል ነው የሚሉ አሉ። ሁለቱም ባለሥልጣናት በተለያዩ ስብሰባዎች ላይ የሚሰጡትን ሃሳቦችና መመሪያዎች በግልጽ መድረክ ላይ የሚቃወሙ እየበረከቱ መጥተዋልም ይባላል።
ህወሃት ሁለቱንም ሰዎች ወደ ክልሉ ሥልጣን ለመመለስ የተለያዩ ሴራዎችን እየሸረበም እንደሆነ የሚገልጹ አሉ።
(ትንሳኤ ራድዮ እንደዘገበው)
Average Rating