በአገሪቱ ሰላምን ለማስፈን በሚካሄደው እንቅስቃሴ ውስጥ ከፖለቲካ ድርጅቶች ይልቅ ሕዝቡን ማሳተፍ እንደሚያስፈልግ፣ ሕዝቡን ያላሳተፈ እንቅስቃሴም ወደ ውድቀት ሊያመራ እንደሚችል የአማራ ህልውና ለኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (አህኢድ) አስታወቀ፡፡
የመላው አማራ ሕዝብ ድርጅት (መአሕድ) እና የአማራ ህልውና ለኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (አህኢድ) በጋራ ለመሥራት የሚያስችላቸውን የመግባቢያ ሰነድ ሰኞ ታኅሳስ 22 ቀን 2011 ዓ.ም. መፈረማቸውን አስመልክተው የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል አቶ ተስፋዬ መኮንን ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ሕዝቡ ከተለያዩ ተፅዕኖዎች ነፃ ከወጣ በፍላጎቱ ላይ የመወሰን ብቃት አለው፡፡
ስለዚህ ለሕዝቡ ነፃነት መስጠት እንደሚገባ፣ ነፃነት ማለት ደግሞ ሰላም መስጠት እንደሆነና ነፃነት በታፈነ ቁጥር ሰላም እንደሚጠፋም አቶ ተስፋዬ አክለዋል፡፡
በትግራይና በአማራ ሕዝብ መካከል ዛሬ እንደሚባለው ሳይሆን ከጥንት ጊዜ ጀምሮ ሲያያዝ የመጣ የጋራ ባህል፣ ፍቅርና አንድነት እንዳለ አቶ ተስፋዬ አመልክተው፣ ይህ ዓይነቱን ጤናማና ወንድማዊ ግንኙነትን ያፈረሰው የተሳሳተ የመስፋፋት አካሄድ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡
‹‹የመስፋፋት አካሄድ ካልቆመ ዕልቂት ያስከትላል፣ በኦሮሚያና በሶማሌ ወገኖቻችን መካከል የተካሄደውም ዕልቂት የዚሁ አባዜ ነው፤›› ያሉት የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባሉ፣ ከዚህ አባዜ መውጣት እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡
የአማራ ህልውና ለኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት ከሁለት ዓመት በፊት በዋሽንግተን ዲሲ መቋቋሙንና በካናዳ፣ በአውስትራሊያና በአንዳንድ የአውሮፓ አገሮች ቅርንጫፎች እንዳሉት አቶ ተስፋዬ አስረድተዋል፡፡
በዋቢ ሸበሌ ሆቴል የስብሰባ አዳራሽ በተከናወነው የፊርማ ሥነ ሥርዓት ላይ ሁለቱም ድርጅቶች የጋራ መግለጫ አውጥተዋል፡፡ ኢትዮጵያ ሉዓላዊና አንድነቱን የጠበቀ ሕዝብ አገር ሆና እንድትፀና ከሚታገሉ፣ ዘረኝነትንና የዘር ማጥፋትን ወንጀል በፅኑ ከሚኮንኑ ሌሎች ድርጅቶች ጋር ኅብረቱ አብሮ ለመሥራት ዝግጁ መሆኑም በመግለጫው ተጠቁሟል፡፡
የጋራ መግለጫው ኢትዮጵያ በአስቸጋሪ የሽግግር ወቅት ውስጥ እንደምትገኝና ዩኒቨርሲቲዎችም የትምህርት ማዕድ መሆናቸው ቀርቶ ሽብር የሚነዛባቸው እንደሆኑ አመልክቶ፣ ይህን የሽብር ድርጊት ሥር ሳይሰድና ሕዝባዊ ዕልቂት ሳያስከትል መንግሥት ሕዝቡን በማስተባበር በአስቸኳይ እንዲያስቆም አሳስቧል፡፡
የኢትዮጵያን የሽግግር ሒደት እደግፋለሁ፣ በሰላማዊ መንገድ እታገላለሁ ብሎ ቃል የገባ ማንኛውም የፖለቲካ ድርጅት ኃላፊነቱን በተሟላ መንገድ፣ ፕሮግራሙን ሰላማዊ በሆነ መንፈስ ለኅብረተሰቡ ማስተላለፍ ይጠበቅበታል የሚል የፀና እምነት እንዳላቸውም ድርጅቶቹ በመግለጫቸው አስረድተዋል፡፡
Average Rating